ሼህ አሊ ጎንደር በኢትዮጵያ የእስልምና ታሪክ ትልቅ ሚና የነበራቸው ሰው ነበሩ
የተወለዱትም #ወሎ ሲሆን ጎንደር ውስጥ በሰሩት ስራ ምክንያት መጠሪያቸው ሼህ
አሊ ጎንደር በመባል በታሪክ ይታወቃሉ።
ሼህ አሊ-ጎንደር በወሎ ክፍለ ሀገር ወረሂምኖ ኮሬብ አከባቢ ‹ምጥግና› ከተባለች
መንደር ነዉ ዉልዳቸዉ ፤ እስከ ጉርምስና ጊዜያቸው በተወለዱበት ሀገር እንደቆዩባት
ይታመናል በ‹የለምድ-ሹም› ማዕረግ ተሹመዉ እንዳስተዳደሩ ይነገራል፡፡
የሀይማኖት መምህር ..የህግአዋቂ...የፍልስፍና ሰው...የመፅሐፍ ደራሲ ብዙ ብዙ
ናቸው።
ጎንደር የባህል፣ የታሪክና የቅርስ መዲና መሆኗ ተደጋግሞ ይጠቀሳል፡፡ ከፋሲል ቤተ
መንግስት እስክ አጼ ፋሲል መዋኛ፣ ከቁስቋም እስከ ደብረ ብርሀን ስላሴ፣ ከጎባጢት
ድልድይ እስከ ወለቃ መንደር በርካታ ታሪካዊና ባህላዊ ሀብቶችን እንዲሁም
ሀይማኖታዊ እሴቶች የያዘች ድንቅ ከተማ ነች፡፡
ከጎንደር ቀደምት መንደሮች መካከል አንዱ አዲስ ዓለም ነው፡፡ አዲስ አለም
ከእስልምና ሀይማኖት ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው መንደር ሲሆን በዘመነ መሳፍንት
መጨረሻ እና በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን መጀመሪያ እንደነበሩ የሚነገርላቸው ታላቁ ወልይ
ሸህ አሊ ጎንደር መስጅድ እና የመቃብር ስፍራ የሚገኝበት ቦታ ነው፡፡
ከ800 ዓመታት በላይ በህይወት እንዳሳለፉ በአፈ ታሪክ የሚነገርላቸው የሸህ አሊ
ጎንደር መስጅድና መካነ መቃብር ከእርሳቸው ጋርም በርካታ ዓመታትን ያስቆጠሩ
የእስልምና ሀይማኖት የእውቀት አባቶች መቃብር ይገኛል፡፡ ታሪካዊ ሁኔታውን በደንብ
አጥንቶና መረጃውን አጠናክሮ ለማስቀመጥ የምሁራንን ጥናት የሚፈልግ ቢሆንም
በበርካታ የእምነቱ ተከታዮች የሚጎበኘው ይህ አካባቢ ድንቅ ተፈጥሯዊ ገጽታን ከታሪክ
ጋር አጣምሮ የያዘ ነው፡፡
ሼህ አሊ ጎንደር ጀበርትይ ! ለሂወታቸዉ በፍፁም ባለመሰሰት ላይ የተከሉት ፤
ተግባራዊ ነብየ-ፍቅራቸዉ በአርእያነቱ ለአፍቃሪያኖች ሕሊናን ቀርፆ አልፏል ፡፡ በሄዱበት
ዓለም ሁሉ ተከበዋል ፡፡ እንባን ከሚያስረጩና የደረቀ ቀልብን ከሚያርሱ ግጥሞቻቸዉና
ምክሮቻቸዉ ለማዳመጥና ለመታደም ብለዉ አያሌዎች ተጋፍተዋል ፡፡
• አምልኮን በማሳመር እና ዓለማዊነትን በመናቅ የተኮተኮቱም ናቸዉ ፡፡ አስደናቂ ገለፃ ፤
ጥበባዊ ንግግራቸዉና ድንቅ አባባላቸዉ ዘመናትን ገና መሻገር ይችላሉ ፡፡ ምክራቸዉ
ልብን ያርዳል ፡፡ ተግሳፅና መንፈሳዊ ቁንጠጣቸዉ የጨቀየን ልቦናና አእምሮን
ያጥራራል ፡፡ በንግግራቸዉ ፤ አላህን በመፍራትና በኢባዳ በመበርታት ወደር
እንዳልነበራቸዉ ቁልጭ ብሎ ይስተዋላሉ ፡፡
የበዙ መንፈሳዊ እዉቀቶችን አካብተዋል ፡፡ በአረብኛ ሰዋሰዉና ፅህፈት ላይ ብሎም
በፍልስፍና ዘርፎች ታታሪነታቸዉንና ብቁነታቸዉን መፃህፍቶቻቸዉ ላይ አስመስክረዋል ፡፡
• ይበልጥ ግን ‹‹ ረሱሉን ›› ለተፈቃሪነት ከፍ አድርጎ ማጉላትና በፍቅራቸዉ መጠመድን
እንደርሳቸዉ የቻለና የተሳካለት እንዳልነበረ በአንድ ድምፅ ሊቃዉንቶች በየጊዜዉ
አስተጋብተዋል ፡፡
.‹‹ እኔን በነቢ ሁብ አንድ የለኝም አጋር
አህመደል ሐዲና ‹አሊ-ጎንደር›ሲቀር ››
በሚሉ ስንኞችም ፤ ምጡቁ ሼኽ ጫሌ ክብራቸዉን ገልፀዋል ፡፡. . . . .
• ሼኽ አሊ-ጎንደር ፍቅራቸዉን በቃል ከመግለፅ ጀምረዉ ፤ በእዉነታቸዉና በምኞታቸዉ
መሃል መንታነትን ዘርተዉ አልፈዋል ፡፡ በዚህ ተዳብሏቸዉ ግር የተሰኙ የዘመናቸዉ
ወዳጆች(ሸሪፍ አብዱል ዓዚዝ/1852 ያረፉ)ና ከዛ በሗላ የመጡ ጠቢባንም ጭምር ፤
ሼኽ አሊ-ጎንደር ማለት ‹‹ ዳግማዊ ዓሊ ቢን አቢጧሊብ ›› ናቸዉ እስከማለት ከፍ
ያሉም ነበሩ ፡፡
በሌላ ረገድ በተሳካ የስነ-ግጥም ታሪክ ገናናና ጥቂት ከነበሩት ሀገር በቀል
ሊቃዉንቶቻችን ዉስጥም ተጠቃሽ ናቸዉ ፡፡ ከመቶዎቹ ዓመታት በፊት የኖሩት ሼህ
አሊ-ጎንደር ፤ አሁንም ድረስ በመላ ሀገሪቱና አንዳንድ የአለም ሀገራት ዘንድ ከፍተኛ
አድናቆትን እያተረፉ ባሉበት ዘመን ተሻጋሪ ፤ ነብያዊ የፍቅር ግጥሞቻቸዉ ነዉ
የሚታወቁትም ፡፡
መንፈስን መጋቢና ስልታዊ ገለፃዎችን ፤ ፍቅር በሚባል ስልቻ ዉስጥ ደንጉረዉ ሰራፂ
በሆኑ ግጥሞቻቸዉ ከሀገራችን የወጡ ናቸዉ ፡፡ በዚሁ ስራቸዉ አማካይነት ከዚያን ጊዜ
ወዲህ ባለዉ የአገራችን ታሪክ ዉስጥ ዝናን እንደናኙ መቀጠልንና በተከታታይ አዳዲስ
ትዉልዶች ፊት ፤ መለኮታዊ ግርማ ሞገስ ሳይለያቸዉ መኖራቸዉን ልብ ብለን ስንረዳ
ደግሞ ፤ የወሎዉን ተወላጅ ሼህ አሊ ጎንደርን በእርግጥም ታላቅ የጥበብ ነፍስ
የታደሉ ሰዉ እንደነበሩ ጩኸን እንመሰክራለን